1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የ2006 የኢትዮጵያ ዓበይት ፖለቲካዊ ክንዉኖች

ሰኞ፣ ጳጉሜን 3 2006

በመሐሉ ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለማርያም ከመስከረም በፊት፤መስከረምና ከዚያ በሕዋላ እሳቸዉም ሹማምንቶቻቸዉም ያሉትን ኢሕአዴግ ሥልጣን የያዘበት ሃያ-ሰወስተኛ ዓመት ሲከበር ደገሙት።ግንቦት ሃያ።ተደጋጋሚዉ ዛቻ፤ እገታ የዚያን ቀን ሰነዓ ላይ ከተፈፀመዉ ያደርሳል ብሎ የጠረጠረ የሩቅ ታዛቢ አልነበረም።ሰኔ አስራ-ስድስት።

https://p.dw.com/p/1D8yQ
ምስል DW

ዘመን ተለወጠ።2006።አዲስ ዓመት፤ አዲስ ተስፋ ግን አሮጌ ማስጠንቀቂያ።«የታሠሩት ወንጀሎኞችን ጉዳይ አንስተዉ የሚፈክሩ አንዳድ ወገኖች አሁንም የሐገሪቱን ሕግ እየጣሱ ነዉ።ሊጠነቀቁ ይገባቸዋል።የዚሕን መንግሥት ትዕግሥት መፈታተን ይፈልጋሉ።»

ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለ ማርያም ደሳለኝ።መስከረም 2006። ከተቃዋሚዉም ጎራ በአሮጌዉ ዓመት የነበረዉ ነዉ የቀጠለዉ።ጠቅላይ ሚንስትሩ ቀጠሉ።«እኒያ ግንቦት ሰባት፤ኦብነግ፤ኦነግ እና አሸባብን የመሳሰሉ አሸባሪ ቡድናት በምክርቤታችን በአሸባሪ ድርጅትነት ተፈርጀዋል። ከነዚሕ ቡድናት ጋር ግንኙነት ያለዉ ማንም ሰዉ ይቀጣል።»

አዲሱ ዓመት በአሮጌዉ እርምጃ፤ ቅጣት፤ ተቃዉሞ-ዉግዘት መሐል፤አዲስ ነገር ብልጭ ማድረጉም አልቀረም።መስከረም ማብቂያ።የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መንግሥት በሕማኖታዊ ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን በመቃወም በየመሳጂዱ ማዉገዝ-መቃወማቸዉ ቢያንስ አስራ-ሰባት መሪዎቻቸዉ ከማሳሰር ሌላ ሰሚ አላገኘም።የመንግሥትም እርምጃ ሙስሊሙን ምዕመንን ድምጻችን ይሰማ በሚል ጥቅል መፈክር ሥር ተቃዉሞ አሳደመዉ እንጂ ተቃዉሞዉን አልገታዉም።ለሰወስተኛ ዓመት ቀጠለ።

«መንግሥት አለ።ያዉም በሐይማኖት ጉዳይ ጣልቃ የማይገባ መንግሥት» አሉ ጠቅላይ ሚንስትሩ።ኮፈሌ ነዋሪዎች ለተቃዉሞ አደባባይ የወጡ ቢያንስ አስራ-አንድ ሙስሊም ዉላጅ፤ወዳጅ፤ዘመድ፤ጎረቤቶቻቸዉን ሕይወት በፀጥታ አስከባሪዎች ጥይት በተነጠቁ በወሩ የበረቀዉ 2006 ለአብዛኛዉ ኢትዮያዊ ሙስሊም ከወከባ፤ እስራት፤ድብደባ፤ የዚያኑ ያክል ከተቃዉሞ ጩኸት ያለፈ ብዙም ትዝታ የለዉም።የመጨረሻዉ ትልቅ ተቃዉሞ፤ የተሰማዉ በቅዱሱ የረመዳን ወር አጋማሽ ነበር።አዲስ አበባ አንዋር መስጊድ።ሐምሌ-2006

Äthiopien Ministerpräsident Hailemariam Desalegn
ምስል Getty Images

በሐይማኖት ጉዳይ ጣልቃ የማይገባዉ መንግሥት ፀጥታ አስከባሪዎች ዘገቦች እንደጠቆሙት መስጊድ ገብተዉ የፈነከቱ፤የደበደቡ፤ ያሰሩ ያጋዙትን ሰዉ ብዛት በትክክል የቆጠረዉ ካለ ቤቱ ነዉ።ለተቃዋሚ ፓርቲዎችም አመቱ ብልጭ-ድርግም የሚለዉ የአደባባይ ሰልፍ የቀጠለበት ነበር።

ከ1997 ወዲሕ የመጀመሪያዉን ታላቅ የተቃዉሞ ሠልፍ ታሕሳ ሁለት ሺሕ አምስት አዲስ አበባ ዉስጥ የጠራዉ ሠማያዊ ፓርቲ አመቱ መግቢያ ላይ ለቀጣይ ሠልፍ ሲዘጋጅ አንድ መቶ አባላቱ መታሠራቸዉን እስታወቀ።

አንድነት ለድሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) ጎንደር፤ ደሴን እና ሌሎችንም ከተሞች በሠልፍ አዳርሶ ባዲሱ አመት የመጀሪያ ወር አዲስ አበባ ዉስጥ ደጋፊዎቹን አሠለፈ።ፓርቲዉ «የሚሊዮኖች ድምፅ ለነጻነት» በሚል አብይ መፈክር የከፈተዉ ዘመቻ አካል በሆነዉ ሠልፍ ዋዜማ ግን የያኔዉ የፓርቲዉ ሊቀመንበርና የቀድሞዉ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ዶክተር ነጋሲሶ ጊዳዳን እና የምክር ቤት እንደራሴ አቶ ግርማ ሠይፉን ጨምሮ ከሥልሳ በላይ የፓርቲዉ መሪዎችና አባላት በቁጥጥር ሥር ዉለዉ ነበር።

ተቃዋሚዎች ለዓመቱ ከጠሩት ሠላማዊ ሠልፍ የመጨረሻዉ አንድነትና መኢአድ በጋራ ባሕርዳር ያስደረጉት ነበር።የካቲት።አንድ የአማራ መስተዳድር ባለሥልጣን ሥለ ዓማራ ሕዝብ መጥፎ ነገር መናገራቸዉን በመቃወም ሁለቱ ፓርቲዎች በጠሩት ሠልፍ በብዙ ሺ የሚቆጠር ሕዝብ መካፈሉ ተዘግቧል።ሰልፉ፤ ከባሕዳር በኋላ ተቀዛቀዘ። አንድነት እና መኢአድ በአዲሱ ዓመት አዲስ የጀመሩት የዉሕደት ዉይይት ቀጠለ።የሁለቱ ፓርቲዎች መሪዎች ሲራራቁ፤ሲቀራረቡ፤ ሲወቃቀሱ፤ ሲወያዩም ከርመዉ ሰኔ ላይ የቅድመ ዉሕደት ሥምምነት ተፈራረሙ።

የመኢአድ ፕሬዝዳንት አቶ አበባዉ መሐሪ።ሥምምነቱ የተፈረመዉ ሁለቱ ፓርቲዎች ከዉጪ በመንግሥት ጫና፤ ከዉስጥ በአባላትና ደጋፊዎቻቸዉ ቅሬታ እንደተናጡ ነዉ።የፓርቲዎቹ ወይም የመሪዎቹ ተቃዋሚዎች ሥምነቱ የተፈረመበትን አዳራሽ ከበዉ በፊርማዉ ሥርዓት ላይ ከታደሙት ጋር ተጋጭተዉ ነበርም።

ሥምምነቱ ከተፈረመ ክጥቂት ሳምንታት በሕዋላ ደግሞ አምስት የአንድነት ፓርቲ ባለሥልጣናት የፓርቲዉን ፕሬዝዳንት የኢንጂነር ግዛቸዉ ሽፈራዉን አሠራር በመቃዉም ሥልጣናቸዉን ለቀቁ።ኢንጂነሩ ባለፈዉ ሳምንት እንዳሉት ለቀድሞ ባለሥልጣኖቻቸዉ ቅሬታ እጅ ልሰጡም።የዉሕደቱ ሥምምነት ሲፈረም ሁለቱ ፓርቲዎች በአንድ ወር ጊዜ ዉስጥ ይዋሐዳሉ ነበር የተባለዉ።ዉሕደቱ የለም። 2006ም ላይመጣ ሊሔድ ሰወስት ቀን ቀረው።

Bildergalerie Demonstration Oppositionspartei UDJ in Äthiopien
ምስል DW

የሳዑዲ አረቢያ መንግስት «በሕገ-ወጥ መንገድ የሚኖሩ» ያላቸዉ ኢትዮጵያዉንን ከጥቅምት እስከ ታሕሳስ እየጠረዘ-ካገሩ ሲያባርር ነበር የከረመዉ።በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ተባረዋል።አዲስ አበባን
ጨምሮ በመላዉ ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያዉን እርምጃዉን በሠልፍ አዉግዘዋል።

ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደቀዳሚዎቹ ዓመታት ሁሉ በየሥፍራዉ የሚገኙ ባለሥልጣኖቻቸዉ፤ አባላት፤ ደጋፊዎቻቸዉ በመንግሥት ፀጥታ ሐይላት መዋከብ፤መንጓጠጥ-መገላመጥ፤ መታሠር-መደብደባቸዉን ፅሕፈት ቤቶቻቸዉ መዘጋት-መታሸጋቸዉን ሳያስታዉቁ፤ እርምጃዉን ሳያወግዙ ብቶ-የተሰናበተ ወር የለም።

ጥር-አጋማሽ ኬንያ ላይ የሆነዉ ወይም ሆነ የተባለዉ ግን ለየት ያለ ነበር።በኬንያ መንግሥት ግብዣ ናይሮቢ የገቡ የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አዉጪ ግንባር (ኦብነግ) ባለሥልጣናት ሱልብ አሕመድ እና ዓሊ ሁሴን በኬንያና በኢትዮጵያ ፀጥታ ሐይሎች ታግተዉ ወደ ኢትዮጵያ መጋዛቸዉ ተሰማ።

ከናይሮቢ-የተሰማዉ ጉድ-አጃብ አሰኝቶ ሳያበቃ የኖርዌ ዜግነት ያለቸዉ የቀድሞ የጋምቤላ ርዕሠ-መስተዳድር ኦኬሎ ኦክዋይ ከደቡብ ሱዳን ታግተዉ ወደ ኢትዮጵያ መወሰዳቸዉ ተነገረ።የናይሮቢ ጁባዉ ክስተት ጉድ-አጃኢብ ያሰኝ እንጂ ከዚያ በፊት ለበርካታ አመታት ሰሜን ሱዳን፤ጅቡቲና ኬንያ የተፈፀመ ወይም ተፈጸመ የተባለዉን እግታና ግዘት ለሚያዉቅ በርግጥ አዲስ አልነበረም።

በመሐሉ ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለማርያም ከመስከረም በፊት፤መስከረምና ከዚያ በሕዋላ እሳቸዉም ሹማምንቶቻቸዉም ያሉትን ኢሕአዴግ ሥልጣን የያዘበት ሃያ-ሰወስተኛ ዓመት ሲከበር ደገሙት።ግንቦት ሃያ።ተደጋጋሚዉ ዛቻ፤ እገታ የዚያን ቀን ሰነዓ ላይ ከተፈፀመዉ ያደርሳል ብሎ የጠረጠረ የሩቅ ታዛቢ አልነበረም።ሰኔ አስራ-ስድስት።

አለን የኢትዮጵያ ቴሌቪዝን።አቶ አንዳርጋቸዉ ፅጌ የግንቦት ሰባት የፍትሕና የዴሞክራሲ ፓርቲ ዋና ፀሐፊ እና የብሪታንያ ዜጋ ናቸዉ።ኬንያ፤ጅቡቲ፤ሰሜንና ደቡብ ሱዳን ሲደረግ ብዙም ከቁብ ያልቆጠረዉ፤ በተለይ ሰሜን አሜሪካና አዉሮጳ የሚኖረዉ ኢትዮጵያዊ ፤ እርማጃዉ ሰነዓ ሲደገም ለአደባባይ ሠልፍ ገነፈለ።

ሐምሌ ግም አለ።የኢትዮጵያ መንግሥትም የአንድነት፤የሠማያዊ ፓርቲ እና የአረና ትግራይ አራት ወጣት ግን ከፍተኛ የአመራር አባላትን አሰረ። የነፃ ወይም የግል ፕሬስ ጋዜጠኞች እንደተቃዋሚ ፓርቲ መሪ- አባላት፤ እንደ ሙስሊሞች ሁሉ ሲታሰሩ፤ በአሸባሪነት ፤ ሲከሰሱ፤ሲወነጀሉ ዓመቱ በሌላ ዓመት ሊተካ እዚሕ ደረሰ።ባንድ ጊዜ በርካታ ጋዜጠኞችና የአምደ መረብ ፀሐፍት የታሰሩት ሚያዚያ ነበር።ስድስት የአምደመረብ ፀሐፍትና ስወስት ጋዜጠኞች።

Äthiopien Mulatu Teshome ist neuer Präsident
ምስል Elias Asmare/AFP/Getty Images

የአምስት መፅሄቶችና የአንድ ጋዜጣ ሕትመት የተቋረጠዉ ደግሞ ነሐሴ።የአንዱ መፅሄት አሳታሚ ሕትመቱ ከመቋረጡ ይልቅ ጋዜጠኞች ላይ የደረሰዉ የመንፈስ ስብራት ነዉ-ያሰጋቸዉ።-----ሥጋቱ የባሰባቸዉ እና የቻሉ በርካታ ጋዜጠኞች ተሰደዱ፤ ባንዴ ሰባት።ባለፉት አስራ-አንድ ወራት ክስ-እስራትን ሽሽት የተሰደዱ ጋዜጠኞች ባንዳድ ዘገቦች ግምት ከሃያ-በልጧል።አምንስቲ ኢንተርናሽናል፤ ሒዩማን ራይትስ ዋች፤ ሲፒጄ፤ ድንበር የለሽ ዘጋቢዎችና ሌሎችም ዓለም አቀፍ የመብትና የጋዜጠኞች ሙያ ተሟጋቾች የኢትዮጵያ መንግሥት በተቃዋሚ ፓርቲ አባላት፤በሙስሊሞችና በጋዜጠኞች ላይ የሚወስደዉን እርምጃ በተደጋጋሚ አዉግዘዋል።ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለማርያም ግን «አንተም ራስሕ ከአሸባሪዎች ጋር እንዳትገናኝ » በማለት አስጠነቀቁት፤ የጠየቃቸዉን የዉጪ ጋዜጠኛ----እና ቀጠሉ።

«ጋዜጠኛ ሁን፤ ሐኪም ሁን አስተማሪ ምንም አይነት ሙያ ቢኖርሕ የሙያዉን ሥነ-ምግባር ጠብቀሕ መስራት አለብሕ።ከዚሕ ካለፍ እና ካሸባሪ ቡድናት ጋር ግንኙነት ካለሕ፤ እነዚሕን አሸባሪ ቡድናት ለማገልገል ከተንቀሳቀስክ ና ከሠራሕ መንግሥት ይምረኛል ብለሕ እንዳታስብ።»እያሉ።

ከእሥራት የተረፈዉ፤ እና ያመለጠዉ ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛ ፖለቲከኛ ወይም ተራዉ ወጣት በገፍ የመሰደዱ ዋና ሰበብ ምክንያት የሲፒጄዉ ባልደረባ ቶም ሮድስ እንደሚሉት የፍትሕ እጦት ነዉ።ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ በምታስገነባዉ ግዙፍ የኤሌክትሪክ ሐይል ማመንጫ ግድብ ሰበብ ከግብፅ ጋር የገጠመችዉ እሰጥ አገባ ቀዝቀዝ የማለቱ ዙና የተሰማዉም የአዲስ አበባ ክረምት አየል ባለበት ነሐሴ ነበር።---------የዉሐ፤የመስኖና የሐይል ሚንስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ።ሐሙስ አዲስ ዓመት እንላለን።2007።

Demonstration der Blue Party in Addis Abeba, Äthiopien
ምስል DW

መልካም አዲስ ዓመት።

ነጋሽ መሐመድ

ተክሌ የኋላ